118ኛው ፓትርያርክ መንገድ ላይ ናቸው
ምንጭ :-http://www.danielkibret.com/2012/10/118.html#more
 |
ዐቃቤ መንበር አቡነ ጳኩሚስ ድምጽ ሲሰጡ
|
የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን 118ኛውን ፓትርያርክ የመምረጡ ሂደት ወደ መጨረሻው ምዕራፍ ተሻግሯል፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ መሠረት አዲስ ፓትርያርክ ለመምረጥ አራት ሂደቶችን
ማለፍ ያስፈልጋል፡፡ የጥቆማና ማጣራት፣ የመጨረሻዎቹን አምስት ዕጩዎች የመወሰን፣ ለዕጣ የሚቀርቡትን ሦስት አባቶችን መምረጥና የመጨረሻውን
አባት በዕጣ መምረጥ ናቸው፡፡
በዚሁ መሠረት ከተጠቆሙት ወደ አሥራ ሰባት አባቶች መካከል የማጣራቱና አምስቱን የመወሰኑ ሂደት እጅግ ረዥም ጊዜ የወሰደ
መሆኑ ታውቋል፡፡ ይህ ሂደት ሁለት ከባባድ ችግሮች ተጋርጠውበት ነበር፡፡ የመጀመርያው ፈተና በቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖና ከተጻፈውና
የግብጽ ቤተ ክርስቲያንም ሕግ ከሚደነግገው ውጭ ሀገረ ስብከት ያላቸው አባቶች ራሳቸውን ሳይቀር ለዕጩነት መምረጣቸው፣ ከዚህ በፊት
አንዳንድ ችግሮች ተከስተውባቸው የነበሩ አባቶችም በዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ መግባታቸው ነበር፡፡
ይህ ሁኔታ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖናና ሕግ ጋር የሚጋጭ በመሆኑ ራሳቸውን ከዕጩነት እንዲያገልሉ በአስመራጭ ኮሚቴውና
በቤተ ክርስቲያኒቱ ታላላቅ አባቶችና ሽማግሌዎች የማግባባትና የማረም ሥራ ሲሠራ ነበር፡፡ ለሁለት ጊዜ ያህል ሱባኤ ታውጆ፣ ጳጳሳቱም
ሁሉ ወደ አባ ብሶይ ገዳም ገብተው በጸሎትና በውይይት ችግሩን ለመፍታት ጥረት አድርገዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የተወሰኑት አባቶች
‹እኔ በሺኖዳ መንበር መቀመጥ የለብኝም› እያሉ ራሳቸውን ከዕጩነት አግልለዋል፡፡
ከዚያ በኋላም ቢሆን የዕጩዎቹ ቁጥር በመብዛቱና በምእመናኑም ዘንድ በአንዳንድ ዕጩዎች ላይ ቅሬታ በመፈጠሩ የምርጫ
ኮሚቴው ጊዜ ወስዶ ችግሮቹን ለመፍታት ሞክሯል፡፡ እጅግ የባሰው ሁለተኛውም ፈተና የተጀመረው በዚህ ጊዜ ነበር፡፡
አንዳንድ ዕጩዎች በቴሌቭዥን ፕሮግራም ሳይቀር ልክ እንደ ፖለቲካ ተመራጮች የምረጡኝ ዘመቻ ጀመሩ፡፡ ሕዝቡ ግራ ተጋባ፡፡
ዐቃቤ መንበሩ አባ ጳኩሚስ አንዳንድ ክርስቲያን የቴሌቭዥን ጣቢያዎችን እስከ ማስጠንቀቅ ደረሱ፡፡ በዚህ ጊዜ ምእመናኑና አባቶች
በወሰዱት ቆራጥ አቋምና ግፊት አንዳንድ እጩዎች ከዕጩነት እንዲወጡ ተደረገ፡፡ በመጨረሻም አምስት አባቶች ቀሩ፡፡ በዚህ ሂደትም
አምስት ጳጳሳትና ሰባት መነኮሳት ከዕጩነት ወጡ፡፡ በሂደቱ ከዕጩነት ከወጡት መካከል የሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ አቡነ ቢሾይ፣ የቀድሞው
ፓትርያርክ ረዳት የነበሩት አቡነ ቡትሮስና የመንበረ ፓትርያርኩ ዋና ጸሐፊ አቡነ ዮሐንስ ይገኙበታል፡፡
በግንቦት ወር የተጀመረው 118ኛውን ፓትርያርክ የመምረጡ ሂደት ባለፈው ሰኞ ወደ መጨረሻው ደረጃ ተሸጋግሯል፡፡ ሰኞ
ዕለት በካይሮ አባስያ በሚገኘው የቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ከአምስቱ አባቶች ሦስቱን በድምጽ የመለየት ሂደት ተከናውኗል፡፡
የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ሕግ እንደሚፈቅደው ብቃት ያላቸው የሚባሉት ድምጽ ሰጭዎች ቁጥራቸው 2411 ነው፡፡ እነዚህ
ድምጽ ሰጭዎች በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሥር ያሉ ካህናት፣ የገዳማት ተወካዮች፣ የምእመናን ተወካዮች፣ በግብጽ ፓርላማ ወንበር
ያላቸው የኮፕት ማኅበረሰብ ተወካዮች፣ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተወካዮችና ክርስቲያና ጋዜጠኞችን ያካተተ ነው፡፡